የመርሲሳይዱ ክለብ ሊቨርፑል አዲሱ ዋና አሰልጣኝ አርኔ ስሎት ቡድናቸው እሁድ ትልቅ ኃላፊነት እንደተጣለበት አጽንኦት ሰጥተዋል።
አርኔ ስሎት ሊቨርፑል የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግን ዋንጫ ሲያነሳ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ወቅት እንደነበር በማስታወስ “በዚህ ምክንያት እሁድ ለእኛ ትልቅ ኃላፊነት ነው። ደጋፊዎቻችን በስታዲየም ተገኝተው ደስታችንን በአካል መጋራት አልቻሉም” ብለዋል።
አክለውም “ሁሉም ሰው እሁድ እስኪደርስ በጉጉት እየጠበቀ ነው፤ ሆኖም አሁንም የሚጠብቀን ሌላ ወሳኝ ተግባር አለብን” ሲሉ ቀጣዩን የቶተንሃም ጨዋታ አስፈላጊነት አመልክተዋል።
“ወደዚህ ክለብ በር ስትረግጡ እዚህ የሚጠበቀው ዋንጫዎችን ማሸነፍ ብቻ እንደሆነ ትገነዘባላችሁ” ሲሉ አርኔ ስሎት ስለ ክለቡ የድል ታሪክ እና የደጋፊዎቹ የሚጠብቁትን ገልጸዋል።
የአርኔ ስሎት ቡድን ሊቨርፑል እሁድ ከቶተንሃም ጋር በሚያደርገው ጨዋታ አንድ ነጥብ ብቻ ማግኘት ከቻለ የ2024-2025 የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሻምፒዮንነቱን ያረጋግጣል። በአንጻሩ አርኔ ስሎት ይህንን ዋንጫ ካነሳ የመጀመሪያው ኔዘርላንዳዊ የፕሪሚየር ሊግ አሰልጣኝ በመሆን ታሪክ ሊሰራ ይችላል።