ማንቸስተር ሲቲ የፈረንሳዩን የኦሎምፒክ ሊዮን አማካይ ሪያን ቼርኪን ማስፈረሙን አስታውቋል። ሪያን ቼርኪ ሜዳ ላይ ኳስ ይዞ ሲጫወት ልዩ የግል ተሰጥኦውን በማሳየት ደጋፊዎችን በማዝናናት ይታወቃል።
ሲቲዎች ሶስተኛ ፈራሚያቸውን ይፋ ያደረጉ ሲሆን፣ ቼርኪ በተለያዩ ቦታዎች ተሰልፎ መጫወት የሚችል እና በሁለቱም እግሮቹ የሚጠቀም ተጫዋች ነው። ተጫዋቹ በተጨማሪም በቀኝ እና በግራ በኩል የሚገኙ የቆሙ ኳሶችን ሲወስድ እንደነበር ይታወሳል።
ቼርኪ የመከላከል እና የሚሰጡትን ታክቲካዊ መመሪያዎች አክብሮ ያለመቆየት ችግር ለማሻሻል ጠንክሮ መስራቱ ተገልጿል። የማንቸስተር ሲቲ ደጋፊዎች ከመጀመሪያው ቀን ጀምሮ በሁሉም ነገር ፍጹም የሆነ ተጫዋች ላይመለከቱ ይችላሉ። ይሁን እንጂ ኳስ በመቆጣጠር የተዋጣለት እንደሆነ የተነገረው ቼርኪ ኳስ ሲያገኝ በተጋጣሚ ላይ ጫና በመፍጠር ወደፊት የሚገፋ ተጫዋች ነው።
በቀኝ እና ግራ ፊት መስመር እንዲሁም የአጥቂ አማካይ ሆኖ መጫወት የሚችለው ቼርኪ ለአሰልጣኝ ፔፕ ጋርዲዮላ ተጨማሪ አማራጮችን ይሰጣል።